ዊሊያም ሼክስፒር (ታህሳስ ወር 1564 - ታህሳስ 23 ቀን 1616 እ.ኤ.አ.) በብዙወች ዘንድ ታላቁ የእንግሊዝኛ ጸሃፊ ተብሎ የሚገመት በእንግሊዝ አገር የኖረ ገጣሚ፣ ተውኔት ደራሲ፣ ድራማ አዘጋጅ ነበር። አብዛኛው ተውኔቶቹ ትራጄዲንና ታሪክን የተመረኮዙ ነበሩ። የኮሜዲ ጽሁፎችንም አቅርቧል። የግጥሞቹና ተውኔቶቹ አንኳር ሃሳቦች የሚያጠነጥኑት የፍቅር፣ ቅናት፣ ንዴትና መሰል ጠንካራ ስሜት ያለው ሰው ሰው ስለመሆን ናቸው። ሼክስፒር ጽሁፎቹን የመዘገባቸው በ1590 እና 1613 እ.ኤ.አ. መካከል ነበር።
ስለሼክስፒር ህይወት ብዙ የተመዘገበ ባይኖርም ሚስቱ አና ሃዘዋይ ትባል እንደነበርና ከርሱ በ5 ወይም 6 አመት ትበልጠው እንደነበር ይነገራል። ሼክስፒር 3 ልጆች ነበሩት፣ ሱዛና ሆል፣ ሃምነት ሼክስፒርና ጁዲት ቅኔይ ።[1] በ1592 እ.ኤ.አ. ሼክስፒር ተዋናይ የነበረ ሲሆን፣ በዚሁ ወቅት በተውኔት ደራሲነቱ እውቅናን እያተረፈ የመጣበት ዘመን ነበር። በ1616 እ.ኤ.አ. ሲሞት ሼክስፒር አንዳቸውንም ጽሁፉን አላሳተመመ ነበር፣ ምክንያቱም አይታወቅም። ተውኔቶቹ የታተሙት ከሞተ በኋላ ነበር።
ሼክስፕሪ ከሞተ 150 ዓመት በኋላ ድርሰቶቹን እርሱ አልጻፋቸውም የሚል አስተያየት ብቅ አለ። ለዚህ ምክንያቱ ሼክስፒር ከእንግሊዝ ውጭ ብዙ ስላልተዘዋወረና በድርሰቶቹ ደግሞ ሌሎች አገሮችን፣ ለምሳሌ ጣሊያንን፣ ስፔንን ወዘተ በጥልቅ እንደሚዋቅ ስለሚያሳይ ነበር። ብዙ ተመራማሪወች የሼክስፒርን ድርሰቶች ሼክስፒር እንደጻፋቸው ቢያምንም አሁን ድረስ እርሱ አልጻፈውም የሚል ክርክር ይነሳል።